መዝሙር 92 NASV

ጻድቅ ሰው ሲደሰት

በሰንበት ቀን የሚዘመር መዝሙር፤ ማሕሌት

1 እግዚአብሔርን ማመስገን መልካም ነው፤ልዑል ሆይ፤ ለስምህ መዘመር ጥሩ ነው፤

2 ምሕረትህን በማለዳ፣ታማኝነትህንም በሌሊት ማወጅ መልካም ነው፤

3 ዐሥር አውታር ባለው በገና፣በመሰንቆም ቅኝት ታጅቦ ማወጅ ጥሩ ነው።

4 እግዚአብሔር ሆይ፤ በሥራህ ስለ ተደሰትሁ፣ስለ እጅህ ሥራ በደስታ እዘምራለሁ።

5 እግዚአብሔር ሆይ፤ ሥራህ እንዴት ታላቅ ነው!ሐሳብህስ ምን ያህል ጥልቅ ነው!

6 ደነዝ ሰው ይህን አያውቅም፤ነኁላላም አያስተውለውም።

7 ክፉዎች እንደ ሣር ቢበቅሉ፣ክፉ አድራጊዎች ቢለመልሙ፣ለዘላለሙ ይጠፋሉ፤

8 እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ግን ለዘላለም ልዑል ነህ።

9 ጠላቶችህ እግዚአብሔር ሆይ፤ ጠላቶችህ ይጠፋሉና፤ክፉ አድራጊዎችም ሁሉ ይበተናሉ።

10 የእኔን ቀንድ ግን እንደ አውራሪስ ቀንድ ከፍ ከፍ አደረግኸው፤በለጋ ዘይትም አረሰረስኸኝ።

11 ዐይኖቼ የባላንጦቼን ውድቀት አዩ፤ጆሮዎቼም የክፉ ጠላቶቼን ድቀት ሰሙ።

12 ጻድቃን እንደ ዘንባባ ይንሰራፋሉ፤እንደ ሊባኖስ ዝግባም ይንዠረገጋሉ።

13 በእግዚአብሔር ቤት ተተክለዋል፤በአምላካችንም አደባባይ ይንሰራፋሉ።

14 ባረጁ ጊዜ እንኳ ያፈራሉ፤እንደ ለመለሙና እንደ ጠነከሩም ይኖራሉ።

15 “እግዚአብሔር ትክክለኛ ነው፤እርሱ ዐለቴ ነው፤ በእርሱ ዘንድ እንከን የለም” ይላሉ።