መዝሙር 31 NASV

የመከራ ጊዜ ጸሎት

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ በአንተ ተተግኛለሁ፤እንግዲህ ዕፍረት ከቶ አይድረስብኝ፤በጽድቅህም ታደገኝ።

2 ጆሮህን ወደ እኔ መልሰህ ስማኝ፤ፈጥነህ አድነኝ፤መጠጊያ ዐለት ሁነኝ፤ታድነኝም ዘንድ ምሽግ ሁነኝ።

3 አንተ ዐለቴና መጠጊያዬ ነህና፣ስለ ስምህ ስትል ምራኝ፤መንገዱንም ጠቍመኝ።

4 አንተ መጠጊያዬ ነህና፣በስውር ከተዘረጋብኝ ወጥመድ አውጣኝ።

5 መንፈሴን በእጅህ ዐደራ እሰጣለሁ፤ እግዚአብሔር የእውነት አምላክ ሆይ፤አንተ ተቤዠኝ።

6 ለከንቱ ጣዖታት ስፍራ የሚሰጡትን ጠላሁ፤ነገር ግን በእግዚአብሔር ታመንሁ።

7 በምሕረትህ ደስ እሰኛለሁ፤ ሐሤትም አደርጋለሁ፤መከራዬን አይተሃልና፤የነፍሴንም ጭንቀት ዐውቀሃል።

8 ለጠላት አሳልፈህ አልሰጠኸኝም፤ነገር ግን እግሮቼን ሰፊ ቦታ ላይ አቆምሃቸው።

9 እግዚአብሔር ሆይ፤ በመከራ ውስጥ ነኝና ማረኝ፤ዐይኖቼ በሐዘን ደክመዋል፤ነፍስና ሥጋዬም ዝለዋል።

10 ሕይወቴ በመጨነቅ፣ዕድሜዬም በመቃተት ዐለቀ፤ከመከራዬ የተነሣ ጒልበት ከዳኝ፤ዐጥንቴም በውስጤ ሟሟ።

11 ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ፣ለጎረቤቶቼ መዘባበቻ፣ለወዳጆቼ መሣለቂያ ሆኛለሁ፤መንገድ ላይ የሚያገኙኝም ይሸሹኛል።

12 እንደ ሞተ ሰው ተረሳሁ፤እንደ ተሰበረ የሸክላ ዕቃም ተቈጠርሁ።

13 የብዙ ሰዎችን ሹክሹክታ እሰማለሁና፤ዙሪያው ሁሉ ሽብር አለ፤በእኔ ላይ ባሤሩ ጊዜ፣ሕይወቴን ለማጥፋት ዶለቱ።

14 እግዚአብሔር ሆይ፤ እኔ ግን በአንተ እታመናለሁ፤“አንተ አምላኬ ነህ” እልሃለሁም።

15 ዘመኔ ያለው በእጅህ ነው፤ከጠላቶቼ እጅ ታደገኝ፤ከሚያሳድዱኝም አድነኝ።

16 ፊትህን በአገልጋይህ ላይ አብራ፤በምሕረትህም አድነኝ።

17 እግዚአብሔር ሆይ፤ወደ አንተ እጮኻለሁና አልፈር፤ክፉዎች ግን ይፈሩ፤ሲኦል ገብተውም ጸጥ ይበሉ።

18 በጻድቁ ላይ በእብሪት የሚናገሩ፣ትዕቢትንና ንቀትን የተሞሉ፣ዋሾ ከንፈሮች ድዳ ይሁኑ።

19 በሰዎች ልጆች ፊት፣ለሚፈሩህ ያስቀመጥሃት፣መጠጊያ ላደረጉህም ያዘጋጀሃት፣በጎነትህ ምንኛ በዛች!

20 ከሰዎች ሤራ፣በማደሪያህ ውስጥ ትሸሽጋቸዋለህ፤ከአንደበት ጭቅጭቅም፣በድንኳንህ ውስጥ ትከልላቸዋለህ።

21 በተከበበች ከተማ ውስጥ፣የሚያስደንቅ ምሕረቱን ያሳየኝ፣ እግዚአብሔር ይባረክ።

22 እኔ በደነገጥሁ ጊዜ፣“ከዐይንህ ፊት ተወግጃለሁ” አልሁ፤አንተ ግን ወደ አንተ ስጮኽ፣የልመናዬን ቃል ሰማህ።

23 እናንተ ቅዱሳኑ ሁሉ፣ እግዚአብሔርን ውደዱት! እግዚአብሔር ታማኞችን ይጠብቃል፤ትዕቢተኞችን ግን ፈጽሞ ይበቀላቸዋል።

24 እግዚአብሔርን ተስፋ የምታደርጉ ሁሉ፤በርቱ፤ ልባችሁም ይጽና።