መዝሙር 132 NASV

የክብረ በዓል መዝሙር

መዝሙረ መዓርግ

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ዳዊትን፣የታገሠውንም መከራ ሁሉ ዐስብ፤

2 እርሱ ለእግዚአብሔር ማለ፤ለያዕቆብም ኀያል አምላክ እንዲህ ሲል ተሳለ፤

3 “ወደ ቤቴ አልገባም፤ዐልጋዬም ላይ አልወጣም፤

4 ለዐይኖቼ እንቅልፍን፣ለሽፋሽፍቶቼም ሸለብታ አልሰጥም፤

5 ለእግዚአብሔር ስፍራን፣ለያዕቆብም ኀያል አምላክ ማደሪያን እስካገኝ ድረስ።”

6 እነሆ፤ በኤፍራታ ሰማነው፤በቂርያትይዓሪም አገኘነው።

7 “ወደ ማደሪያው እንግባ፤እግሮቹ በሚቆሙበት ቦታ እንስገድ።

8 እግዚአብሔር ሆይ፤ ተነሥ፤አንተና የኀይልህ ታቦት ወደ ማረፊያህ ስፍራ ሂዱ።

9 ካህናትህ ጽድቅን ይልበሱ፤ቅዱሳንህም እልል ይበሉ።”

10 ስለ አገልጋይህ ስለ ዳዊት ስትል፣የቀባኸውን ሰው አትተወው።

11 እግዚአብሔር ለዳዊት በእውነት ማለ፤በማይታጠፍም ቃሉ እንዲህ አለ፤“ከገዛ ራስህ ፍሬ፣በዙፋንህ ላይ አስቀምጣለሁ።

12 ወንዶች ልጆችህ ኪዳኔን፣የማስተምራቸውንም ምስክርነቴን ቢጠብቁ፣ልጆቻቸው በዙፋንህ ላይ፣ለዘላለም ይቀመጣሉ።

13 እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፣ማደሪያውም ትሆን ዘንድ ወዶአልና እንዲህ አለ፤

14 “ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ናት፤ፈልጌአታለሁና በእርሷ እኖራለሁ።

15 እጅግ አትረፍርፌ እባርካታለሁ፤ድኾቿን እንጀራ አጠግባለሁ።

16 ለካህናቷ ድነትን አለብሳለሁ፤ቅዱሳኗም በደስታ ይዘምራሉ።

17 “በዚህም ለዳዊት ቀንድ አበቅላለሁ፤ለቀባሁትም ሰው መብራት አዘጋጃለሁ።

18 ጠላቶቹን ኀፍረት አከናንባቸዋለሁ፤እርሱ ግን በራሱ ላይ የደፋው ዘውድ ያበራል።