መዝሙር 105 NASV

የእስራኤል ድንቅ ታሪክ

1 እግዚአብሔርን አመስግኑ፤ ስሙንም ጥሩ፤ሥራውንም በሕዝቦች መካከል ግለጡ።

2 ተቀኙለት፤ ዘምሩለት፤ድንቅ ሥራዎቹንም ሁሉ ተናገሩ።

3 በቅዱስ ስሙ ተጓደዱ፤ እግዚአብሔርን የሚሹት ልባቸው ደስ ይበለው።

4 እግዚአብሔርንና ብርታቱን ፈልጉ፤ፊቱንም ዘወትር ፈልጉ።

5 ያደረጋቸውን ድንቅ ሥራዎች፣ታምራቱንና ከአፉ የወጣውን ፍርድ አስቡ፤

6 እናንተ የአገልጋዩ የአብርሃም ዘሮች፣ለራሱም የመረጣችሁ የያዕቆብ ልጆች ሆይ፤ አስታውሱ።

7 እርሱ እግዚአብሔር አምላካችን ነው፤ፍርዱም በምድር ሁሉ ላይ ነው።

8 ኪዳኑን ለዘላለም፣ያዘዘውንም ቃል እስከ ሺህ ትውልድ ያስታውሳል።

9 ከአብርሃም ጋር ያደረገውን ኪዳን፣ለይስሐቅም በመሐላ የተሰጠውን ተስፋ አይረሳም።

10 ይህንም ለያዕቆብ ሥርዐት አድርጎ፣ለእስራኤልም የዘላለም ኪዳን አድርጎ አጸናለት፤

11 እንዲህም አለ፤ “የርስትህ ድርሻ አድርጌ፣የከነዓንን ምድር እሰጥሃለሁ።”

12 በቍጥር አነስተኞች ሆነው ሳሉ፣እጅግ ጥቂትና ባይተዋሮች ሳሉ፣

13 ከሕዝብ ወደ ሕዝብ ሲንከራተቱ፣ከአንዱ መንግሥት ወደ ሌላው ሲቅበዘበዙ፣

14 ማንም ግፍ እንዲፈጽምባቸው አልፈቀደም፤ስለ እነርሱም ነገሥታትን እንዲህ ሲል ገሠጸ፤

15 “የቀባኋቸውን አትንኩ፤በነቢያቴም ላይ ክፉ አታድርጉ።”

16 በምድሪቱ ላይ ራብን ጠራ፤የምግብንም አቅርቦት ሁሉ አቋረጠ፤

17 በባርነት የተሸጠውን ሰው፣ዮሴፍን ከእነርሱ አስቀድሞ ላከ።

18 እግሮቹ በእግር ብረት ተላላጡ፤በዐንገቱም የብረት ማነቆ ገባ።

19 የተናገረው ቃል እስኪፈጸምለት፣ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው።

20 ንጉሥ ልኮ አስፈታው፤የሕዝቦችም ገዥ ነጻ አወጣው።

21 የቤቱ ጌታ፣የንብረቱም ሁሉ አስተዳዳሪ አደረገው፤

22 ይኸውም ሹማምቱን በራሱ መንገድ ይመራ ዘንድ፣ታላላቆቹንም ጥበብ ያስተምር ዘንድ ነበር።

23 እስራኤል ወደ ግብፅ ገባ፤ያዕቆብ በካም ምድር መጻተኛ ሆነ።

24 እግዚአብሔር ሕዝቡን እጅግ አበዛ፤ከጠላቶቻቸውም ይልቅ አበረታቸው፤

25 ሕዝቡን እንዲጠሉ፣በባሪያዎቹም ላይ እንዲያሤሩ ልባቸውን ለወጠ።

26 ባሪያውን ሙሴን፣የመረጠውንም አሮንን ላከ።

27 እነርሱም ታምራታዊ ምልክቶችን በመካከላቸው፣ድንቅ ነገሮቹንም በካም ምድር አደረጉ።

28 ጨለማን ልኮ ምድሪቱን ጽልመት አለበሰ፤እነርሱም በቃሉ ላይ ማመፅን ተዉ።

29 ውሃቸውን ወደ ደም ለወጠ፤ዓሦቻቸውንም ፈጀ።

30 ምድራቸውም፣ የነገሥታታቸው እልፍኝ ሳይቀር፣ጓጒንቸር ተርመሰመሰባቸው።

31 እርሱ በተናገረ ጊዜ የዝንብ መንጋ መጣ፤ትንኞችም ምድራቸውን ወረሩ።

32 ዝናባቸውን በረዶ አደረገው፤ምድራቸውም ሁሉ መብረቅ አወረደ።

33 ወይናቸውንና በለሳቸውን መታ፤የአገራቸውንም ዛፍ ከተከተ።

34 እርሱ በተናገረ ጊዜ አንበጣ መጣ፤ስፍር ቍጥር የሌለውም ኵብኵባ ከተፍ አለ፤

35 የምድሪቱንም ዕፀዋት ሁሉ በላ፤የመሬታቸውንም ፍሬ ሙጥጥ አደረገ፤

36 ደግሞም በአገራቸው ያለውን በኵር ሁሉ፣የኀይላቸውንም ሁሉ በኵራት መታ።

37 የእስራኤልንም ሕዝብ ብርና ወርቅ ጭኖ እንዲወጣ አደረገ፤ከነገዶቻቸውም አንድም አልተደናቀፈም።

38 እጅግ ፈርተዋቸው ነበርና፣ወጥተው ሲሄዱ ግብፅ ደስ አላት።

39 ደመናን እንደ መጋረጃ ዘረጋላቸው፤እሳትም በሌሊት አበራላቸው።

40 በለመኑትም ጊዜ፣ ድርጭት አመጣላቸው፤የሰማይንም እንጀራ አጠገባቸው።

41 ዐለቱን ሰነጠቀ፤ ውሃም ተንዶለደለ፤እንደ ወንዝም በበረሓ ፈሰሰ።

42 ለባሪያው ለአብርሃም የሰጠውን፣ቅዱስ የተስፋ ቃሉን አስቦአልና።

43 ሕዝቡን በደስታ፣ምርጦቹንም በእልልታ አወጣቸው።

44 የሌሎችን ሕዝቦች ምድር ሰጣቸው፤የእነዚህንም የድካም ፍሬ ወረሱ፤

45 ይህም ሥርዐቱን ይጠብቁ ዘንድ፣ሕጉንም ይፈጽሙ ዘንድ ነው።ሃሌ ሉያ።