መዝሙር 107 NASV

አምስተኛ መጽሐፍ

ከመከራ ሁሉ የሚታደግ አምላክ

1 ቸር ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ፤ምሕረቱም ለዘላለም ነውና።

2 እግዚአብሔር የተቤዣቸው፣ከጠላት እጅ የታደጋቸው ይህን ይበሉ፤

3 ከምሥራቅና ከምዕራብ፣ ከሰሜንና ከደቡብ፣ከየአገሩ የሰበሰባቸው እንዲህ ይናገሩ።

4 አንዳንዶቹ ጭው ባለ በረሓ ተቅበዘበዙ፤ወደሚኖሩባት ከተማ የሚያደርስ መንገድ አጡ።

5 ተራቡ፤ ተጠሙ፤ነፍሳቸውም በውስጣቸው ዛለች።

6 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፤እርሱም ከመከራቸው አዳናቸው።

7 ወደሚኖሩባትም ከተማ፣በቀና መንገድ መራቸው።

8 እግዚአብሔርን ስለ ምሕረቱ፣ለሰው ልጆችም ስላደረገው ድንቅ ሥራ ያመስግኑት፤

9 እርሱ የተጠማችውን ነፍስ አርክቶአልና፤የተራበችውንም ነፍስ በበጎ ነገር አጥግቦአል።

10 አንዳንዶቹ በብረት ሰንሰለት ታስረው የተጨነቁ፣በጨለማ፣ በጥልማሞት ውስጥ የተቀመጡ ነበሩ፤

11 በእግዚአብሔር ቃል ላይ በማመፅ፣የልዑልን ምክር አቃለዋልና።

12 ስለዚህ በጒልበት ሥራ ልባቸውን አዛለ፤ተዝለፈለፉ፤ የሚደግፋቸውም አልነበረም።

13 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፤እርሱም ከመከራቸው አዳናቸው።

14 ከጨለማና ከጥልማሞት አወጣቸው፤እስራታቸውንም በጠሰላቸው።

15 እግዚአብሔርን ስለ ምሕረቱ፣ለሰው ልጆችም ስላደረገው ድንቅ ሥራ ያመስግኑት፤

16 እርሱ የናሱን በሮች ሰብሮአልና፤የብረቱንም መወርወሪያ ቈርጦአል።

17 አንዳንዶቹ ከዐመፃቸው የተነሣ ቂሎች ሆኑ፤ከበደላቸው የተነሣ ችግር ውስጥ ገቡ።

18 ሰውነታቸው የምግብ ዐይነት ሁሉ ተጸየፈች፤ወደ ሞትም ደጆች ቀረቡ።

19 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፤እርሱም ከመከራቸው አዳናቸው።

20 ቃሉን ልኮ ፈወሳቸው፤ከመቃብርም አፋፍ መለሳቸው።

21 እግዚአብሔርን ስለ ምሕረቱ፣ለሰው ልጆችም ስላደረገው ድንቅ ሥራ ያመስግኑት፤

22 የምስጋናም መሥዋዕት ያቅርቡለት፤ሥራውንም ደስ በሚል ዝማሬ ይግለጹ።

23 አንዳንዶቹ በመርከብ ወደ ባሕር ወረዱ፤በታላቅም ውሃ ላይ ሥራቸውን አከናወኑ፤

24 የእግዚአብሔርን ሥራ በዚያ አዩ፤ድንቅ አድራጎቱንም በጥልቁ ውስጥ ተመለከቱ።

25 እርሱ ተናግሮ ዐውሎ ነፋስን አስነሣ፤ነፋሱም ማዕበሉን ከፍ ከፍ አደረገ።

26 ወደ ሰማይ ወጡ፤ ወደ ጥልቅም ወረዱ፤ከመከራቸውም የተነሣ ሐሞታቸው ፈሰሰ።

27 እንደ ሰከረ ሰው ዞሮባቸው ወዲያ ወዲህ ተንገዳገዱ፤መላው ጠፍቶባቸው የሚያደርጉትን አጡ።

28 በተጨነቁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፤እርሱም ከመከራቸው አዳናቸው።

29 ዐውሎ ነፋሱን ጸጥ አደረገ፤የባሕሩም ሞገድ ረጭ አለ።

30 ጸጥ በማለቱም ደስ አላቸው፤ወዳሰቡትም ወደብ አደረሳቸው።

31 እግዚአብሔርን ስለ ምሕረቱ፣ለሰው ልጆችም ስላደረገው ድንቅ ሥራ ያመስግኑት፤

32 በሕዝብ ጉባኤ መካከል ከፍ ከፍ ያድርጉት፤በሽማግሌዎችም ሸንጎ ይወድሱት።

33 ወንዞችን ወደ ምድረ በዳ፣የውሃ ምንጮችንም ወደ ደረቅ ምድር ለወጠ።

34 ከነዋሪዎቿ ክፋት የተነሣ፣ፍሬያማዋን ምድር በጨው የተበከለች አደረጋት።

35 ምድረ በዳውን ወደ ውሃ መከማቻ፣ደረቁንም ምድር ወደ ውሃ ምንጭ ቀየረ።

36 የተራቡትን በዚያ አስቀመጠ፤የሚኖሩባትንም ከተማ ሠሩ።

37 በዕርሻውም ዘሩበት፤ ወይንም ተከሉ፤ብዙ ፍሬም አመረቱ።

38 ይባርካቸዋል፤ እነርሱም እጅግ ይበዛሉ፤የከብቶቻቸውም ብዛት እንዲያንስ አያደርግም።

39 በጭንቅ፣ በመከራና በሐዘን፣ቍጥራቸው አንሶ፣ ተዋርደው ነበር፤

40 በመኳንንቱም ላይ መናቅን አዘነበባቸው፤መውጫ መግቢያው በማይታወቅ በረሓ ውስጥም አንከራተታቸው።

41 ችግረኞችን ግን ከጭንቀታቸው መዝዞ አወጣቸው፤ቤተ ሰባቸውንም እንደ በግ መንጋ አበዛ።

42 ልበ ቅኖች ይህን አይተው ሐሤት ያደርጋሉ፤ጥመትም ሁሉ አፏን ትዘጋለች።

43 እንግዲህ ማንም ብልህ ቢሆን፣ ይህን ነገር ልብ ይበል፤እርሱም የእግዚአብሔርን ምሕረት ያስተውላል።