መዝሙር

ምዕራፎች 90

መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም

አራተኛ መጽሐፍ

የሰው ልጅ ሕይወት

የእግዚአብሔር ሰው የሙሴ ጸሎት

1 እግዚአብሔር ሆይ፤አንተ ከትውልድ እስከ ትውልድ መጠጊያችን ሆንህልን። 2ገና ተራሮች ሳይወለዱ፣ምድርንና ዓለምን ከመፍጠርህ በፊት፣አንተ ከዘላለም እስከ ዘላለም አምላክ ነህ። 3ሰዎችን ወደ ዐፈር ትመልሳለህ፤“የሰው ልጆች ሆይ፤ ወደ ቦታችሁ ተመለሱ” ትላለህ፤ 4ሺህ ዓመት በፊትህ፣እንዳለፈችው እንደ ትናንት ቀን፣እንደ ሌሊትም እርቦ ነውና። 5እንደ ጐርፍ ጠርገህ ስትወስዳቸው፣ እንደ ሕልም ይበናሉ፤እንደ ማለዳ ሣር ታድሰው ይበቅላሉ፤ 6ሣሩም ንጋት ላይ አቈጥቍጦ ይለመልማል፤ምሽት ላይ ጠውልጎ ይደርቃል። 7በቊጣህ አልቀናልና፤በመዓትህም ደንግጠናል። 8በደላችንን በፊትህ፣የተሰወረ ኀጢአታችንንም በገጽህ ብርሃን ፊት አኖርህ። 9ዘመናችን ሁሉ በቊጣህ ዐልፎአልና፤ዕድሜአችንንም በመቃተት እንጨርሳለን። 10የዕድሜአችን ዘመን ሰባ ዓመት፣ ቢበዛም ሰማንያ ነው፤ከዚያ በላይ ከሆነም ድካምና መከራ ብቻ ነው፤ቶሎ ያልፋልና፤ እኛም ወዲያው እንነጒዳለን። 11የቍጣህን ኀይል ማን ያውቃል?መዓትህም የመፈራትህን ያህል ታላቅ ነው። 12ጥበብን የተሞላ ልብ ይኖረን ዘንድ፣ዕድሜያችንን መቍጠር አስተምረን። 13 እግዚአብሔር ሆይ፤ ተመለስ፤ ይህ እስከ መቼ ይሆናል?ለአገልጋዮችህም ራራላቸው። 14በዘመናችን ሁሉ ደስ እንዲለን፣ ሐሤትም እንድናደርግ፣ምሕረትህን በማለዳ አጥግበን። 15መከራ ባሳየኸን ዘመን መጠን፣ክፉም ባየንባቸው ዓመታት ልክ ደስ አሰኘን። 16ሥራህ ለአገልጋዮችህ፣ክብርህም ለልጆቻቸው ይገለጥ። 17የጌታ የአምላካችን ሞገስ በላያችን ይሁን፤የእጆቻችንን ሥራ ፍሬያማ አድርግልን፤አዎን፣ ፍሬያማ አድርግልን።