መዝሙር 30 NASV

ከክፉ አደጋ የዳነ ሰው ምስጋና

ለቤተ መቅደሱ ምረቃ የተዘመረ፤ የዳዊት መዝሙር

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ከታች አንሥተኸኛልና፣ጠላቶቼም በላዬ እንዳይደሰቱ አድርገሃልና፣ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ።

2 እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ፤ ትረዳኝ ዘንድ ወደ አንተ ጮኽሁ፤አንተም ፈወስኸኝ።

3 እግዚአብሔር ሆይ ነፍሴን ከሲኦል አወጣሃት፤ወደ ጒድጓድ ከመውረድም መልሰህ ሕያው አደረግኸኝ።

4 እናንተ ቅዱሳኑ፤ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ቅዱስ ስሙንም አወድሱ።

5 ቊጣው ለዐጭር ጊዜ ነው፤ቸርነቱ ግን እስከ ዕድሜ ልክ ነውና፤ሌሊቱን በልቅሶ ቢታደርም፣በማለዳ ደስታ ይመጣል።

6 እኔም በተረጋጋሁ ጊዜ፣“ከቶ አልናወጥም” አልሁ።

7 እግዚአብሔር ሆይ፤ በአንተ ሞገስ፣ተራሮቼ ጸኑ፣ፊትህን በሰወርህ ጊዜ ግን፣ውስጤ ታወከ።

8 እግዚአብሔር ሆይ፤ ወደ አንተ ተጣራሁ፤ወደ ጌታም እንዲህ ብዬ ጮኽሁ፤

9 “በእኔ ወደ ጒድጓድ መውረድ፣በመሞቴ ምን ጥቅም ይገኛል?ዐፈር ያመሰግንሃልን?ታማኝነትህንስ ይናገራልን?

10 እግዚአብሔር ሆይ፤ ስማ፤ ማረኝም፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ ረዳት ሁነኝ።”

11 ዋይታዬን ወደ ሽብሸባ ለወጥህልኝ፤ማቄን አውልቀህ ፍስሓን አለበስኸኝ፤

12 እንግዲህ ነፍሴ ታመስግንህ፤ ዝምም አትበል፤ እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ፤ ለዘላለም አመሰግንሃለሁ።